የሐረ ሸይጣን ሐይቅ የሚገኘው በስልጤ ዞን በስልጢ ወረዳ በአጎዴቀበሌ ሲሆን ከዞኑ ዋና ከተማ ወራቤ በስተሰሜን አቅጣጫ በ30.4ኪ/ሜትር ርቀት ላይ ከዋናው አ.አ ወራቤ፣አርባምንጭ በተዘረጋው አስፓልት መንገድ በስተምስራቅ 1.2 ኪ/ሜ እንዲሁም ከቡታጅራ ከተማ 9 ኪ/ሜ ጉዞ በኋላ ስልጤ ዞን እንደገቡ የሚያገኙት ሐይቅ ነዉ፡፡ ከወረዳው ዋና ከተማ ቅበት ደግሞ በ3.4 ኪ/ሜ ርቀት ላይ ነው የሚገኘዉ፡፡ ሀይቁ በተፈጥሯዊና ታሪካዊ ይዘቱ፣በአፈጣጠሩና በጎብኚዎች ዘንድ በሚያሳድረው አግራሞት ከሁሉም ዓይነት ሐይቆች የሚለይና ተመልካችን የሚያረካና የሚያዝናና ሆኖ ይገኛል፡፡ ኃይቁ በአፈጣጠሩ ከላይኛው የመሬት ገፅታ በታች የሚገኝ ሆኖ የገበቴ ቅርፅ ያለው ፣ከለሩንም በየጊዜው የሚቀያይር አስደናቂና በክልሉ ሌላ ቦታ የሌለ ሀይቅ ነው፡፡ ሐይቁን በሚጎበኙ ቱሪስቶች ሐይቁ በሚገኝበት ዳገት አፋፍ ላይ በመሆን ጠብ ሲል የማይታየዉን ድንጋይ/ጠጠር ወርዉሮ ለማስገባት የሚደረገው ትዕይንት የበለጠ ያዝናናል፡፡ የሀረ-ሸይጣን ሀይቅን 1ኪ/ሜ ገደማ አለፍ ሲሉ የአይናጌ ዋሻን ከአስገራሚ ሁኔታዎች ጋር ያገኙታል፡፡ በሀረ-ሸይጣን ሀይቅ አካባቢ የሚደረግ ጉብኝትና ልዩ የመዝናኛ ፕሮግራም በማይለቅ ብዕር የሚጻፍ የህሊና ላይ ታሪክ እንደሆነ ብዙዎች መስክረዋል፡፡